News Detail
May 19, 2025
12 views
የትምህርት ዘርፉን አገራዊ ሪፎርም መሰረት በማድረግ ስራዎችን መስራት እንደሚገባ ተጠቆመ። በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የለውጥና የሪፎርም አጀንዳዎች ዙሪያ ውይይት ተደርጓል።
የስራ አመራር መሪ ስራ አስፈጻሚ ይበልጣል አያሌው (ዶ/ር) በዚሁ ጊዜ እንደገለጹት የአገር አቀፍ ሪፎርም አካል የሆነው የትምህርት ዘርፍ ሪፎርም በሙከራ ደረጃ ወደ ስራ ይገባል።
በሙከራ ደረጃ ወደ ስራ ለሚገባው የሪፎርም ትግበራ የመዋቅርና የአሰራር ስርዓት ማሻሻያ እየተደረገ እንደሆነም ዶክተር ይበልጣል አክለው ገልጸዋል።
የአሰራር ማሻሻያውን ተከትሎም አዋጆች፣ ደንቦችና መመሪያዎች በአዲስ መልኩ ተሻሽለው እንዲዘጋጁ መደረጉንም ተናግረዋል።
የሙከራ ትግበራው በቅድሚያ በትምህርት ሚኒስቴርና ተጠሪ ተቋማት ከዚያም ከከፍተኛ ትምህርት ተቋማት እስከ ትምህርት ቤቶች ደረጃ በደረጃ በተግባራዊ እንደሚደረግ አመልክተዋል።
በከፍተኛ ትምህርት ልማት ዘርፍ የምርሞርና የማህበረሰብ ጉድኝት ጉዳዮች መሪ ስራ አስፈጻሚ ሠራዊት ሀንዲሶ ዶ/ር) በበኩላቸው በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የሚካሄዱ ሪፎርሞች ተቋማቱ ተልኳቸው በአግባቡ እንዲወጡ እንደሚያስችል ተናግረዋል።
የዩኒቨርስቲዎች ዓላማ ማህበረሰብን መለወጥ መሆኑን የጠቆሙት ዶክተር ሠራዊት ተቋማቱ ያሉባቸውን የአሰራር ተግዳሮቶች በመለየት በአፋጣኝ መፍታት እንደሚጠበቅባቸውም ጠቁመዋል።
የተቋማዊ ለውጥ ስራ አስፈጻሚ አቶ ከበደ ግዛው በበኩላቸው በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የሚካሄዱ የሪፎርም አጀንዳዎች ተቋማዊ ሊሆኑ እንደሚገባ አስረድተዋል።
የውይይት መድረኩ ዓላማ በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የለውጥ ስራዎች የመልካም አስዳደርና የሪፎርም አጀንዳዎች የአሰራር ስርዓት ማስፈጸሚያ ስትራቴጂ ለመገምገም መሆኑንም አቶ ከበደ ጨምረው ገልጸዋል።