News Detail

National News
Jul 29, 2024 1.7K views

ሀገር እንዲጸናና የትውልድ ቅብብሎሽ እንዲኖር የመምህራን ሚና ከፍተኛ መሆኑን የኢፌዲሪ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር ክቡር ዐብይ አህመድ ገለጹ።

የ60 ሺ መምህራናና የትምህርት ቤት አመራሮች ልዩ የክረምት የአቅም ማጎልበቻ ስልጠና መክፈቻ መርሃ ግብር ተካሄዷል።
የኢ.ፌ.ድ.ሪ ጠቅላይ ሚኒስትርክቡር ዶ/ር ዐብይ አህመድ በመርሃ ግብሩ ማስጀመሪያ ላይ በበይነ መረብ ባስተላለፉት መልዕክት ሀገር እንዲጸናና የትውልድ ቅብብሎሽ እንዲኖር የመምህራን ሚና ከፍተኛ መሆኑን ገልጸዋል።
ስልጠናው የትምህርት ጥራት ለማረጋገጥ የተጀመሩ ሥራዎችን የሚያግዝና መምህራን በሚያስተምሩት ትምህርትና የማስተማሪያ ስነ ዘዴ ላይ ተጨማሪ አቅም ማበልጸጊያ መሆኑንም ጠቅሰዋል።
መንግስት በመምህራን ዘንድ የሚስተዋለውን የኑሮ ጫና ለመቀነስ አቅም በፈቀደ መጠን ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ መሆኑንም ጠቅላይ ሚኒስትሩ በመልዕክታቸው አንስተው በቅርቡ እንደ ሀገር የተደረገው የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያም የኢትዮጵያን ኢኮኖሚ ከታሰረበት እንደሚፈታው አመላክተዋል።
መምህራን የጸናችና የበለጸገች ኢትዮጵያ እንድትኖር አይተኬ ሚና እንዳላቸው ገልጸው ትውልዱ ህዝብና ሀገሩን እንዲወድ፣ እርዳታና ልመናን የሚጠየፍ እንዲሆን ሙያዊ ሀላፊነታቸውን እንዲወጡ መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል።
የትምህርት ሚኒስትሩ ክቡር ፕ/ር ብርሃኑ ነጋ በበኩላቸው የትምህርት ጥራትን ለማረጋገጥ የመምህራንን አቅም ማሳደግ ወሳኝ መሆኑን ጠቅሰው በ28 የኒቨርሲቲዎች ከሁሉም የሀገሪቱ 2ኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ለተውጣጡ ከ60 ሺ ለሚበልጡ መምህራናና የትምህርት ቤት ዳይሬክተሮች የሚሰጥ ስልጠና መሆኑን ጠቅሰዋል።
ስልጠናው እንደ ሀገር የገጠመንን የትምህርት ጥራት ችግር ለመፍታት ከሚሰሩ ሥራዎች መካከል አንደኛው መሆኑን ጠቅሰው ከፖለቲካ ጋር ያልተገናኘና ሙያ እና የማስተማሪያ ሥነ ዘዴ ላይ ብቻ ትኩረት ያደረገ መሆኑንም አብራርተዋል።
ይህን ስልጠና በአግባቡ ተከታትለው ላጠናቀቁና ከ70 በመቶ በላይ ውጤት ለሚያስመዘግቡ መምህራናና የትምህርት ቤት ዳይሬክተሮች ሰርተፊኬት እንደሚሰጥ ጠቅሰው በቀጣይ በደረጃ እድገትና በሌሎች የማትጊያ ሥርዓቶች ጥቅም ላይ እንደሚውል አመላክተዋል።
ዘንድሮ በ60 ሺ መምህራናና የትምህርት ቤት ዳይሬክተሮች የተጀመረው ስልጠና በቀጣዮቹ ሦስት ዓመታት ለሁሉም የመጀመሪያና ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት መምህራንና ዳይሬክተሮች የሚሰጥ መሆኑን ጠቅሰዋል።
የአጠቃላይ ትምህርት ልማት ዘርፍ ሚኒስትር ዴኤታ ክብርት ወ/ሮ አየለች እሸቴ በበኩላቸው ትምህርት ሚኒስቴር ለዚህ ስልጠና በቂ ዝግጅት ማድረጉን ገልጸው ለስልጠናው የማስተባበር ሀላፊነት የተሰጣችሁ ከዩነቨርስቲ አመራሮችና አሰልጣኞች ጋር በመተባበር በዛሬው እለት ተገቢ ኦረንቴሽን ሰጥታችሁ ነገ ወደ ሙሉ ስልጠና እንዲገባ ሲሉ አሳስበዋል። ይህ የክረምት ስልጠና ፕሮግራም እንዲሳካ ሰልጣኞች ትልቅ ሃላፊነት እንዳለባቸው ገልጸው ሰልጣኞችም ይህንን ሲተገብሩ ስልጠናው አላማውን ይመታል ብለዋል።
በመጨረሻም የሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ ከፍተኛ አመራሮች በየዩኒቨርስቲዎቹ በመዘዋወር የስልጠናውን ሂደት እንደሚከታተሉ ገልጸዋል።
Recent News
Follow Us