News Detail

National News
May 16, 2024 689 views

የዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንቶች ፎረም እየተካሄደ ይገኛል።

የኢትዮጵያ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንቶች ፎረም '' የከፍተኛ ትምህርት እጅግ ለላቀ ተፅዕኖ'' በሚል መሪ ቃል በመቐለ ዩኒቨርስቲ አስተናጋጅነት እየተካሄደ ይገኛል።
በፎረሙ መክፈቻ የተገኙት የትምህርት ሚኒስቴር ከፍተኛ ትምህርት ልማት ዘርፍ ሚኒስትር ዴኤታ ክቡር አቶ ኮራ ጡሽኔ በዚህ ፎረም በከፍተኛ ትምህርት ልማት ዘርፍ የተለዩ ቁልፍ የሪፎርም አጀንዳዎችን ለማስቀጠልና ውጤታማ ለማድረግ ውይይት በማድረግ ለዘርፉ ስኬታማነት መሠረት የሚሆን አቅጣጫ ይቀመጣል ብለዋል።
የዩኒቨርሲቲዎች እድገት፣ ስኬትና ውጤት መለካት አለበት ያሉት ሚኒስትር ዴኤታው ለዚህም መለኪያ መስፈርቶች ተዘጋጅተው በዚህ መድረክ ላይ ከስምምነት ተደርሶ ይወጣልም ብለዋል።
የመቀሌ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት ዶ/ር ፋና ሀጎስ በበኩላቸው በትግራይ ከነበረው ችግር በመውጣት ዩኒቨርሲቲው ከ19 ሺ በላይ ተማሪዎችን ተቀብሎ ወደ መማር ማስተማር ሥራ መግባቱና ይህንን ሀገራዊ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የምክክር መድረክ ለማዘጋጀት በመብቃቱ ደስታ እንደተሰማቸው ገልፀዋል ።
የትግራይ ጊዜያዊ አስተዳደር የማህበራዊ ልማት ሽግግር ሴክሬታሪያት ክንደያ ገ/ህይወት(ፕ/ር) ደግሞ በትግራይ ከነበረው ጦርነት ሁላችንም ልንማር ይገባል ያሉ ሲሆን ከፍተኛ ትምህርት ለአንድ ሀገር ልማትና እድገት አስተዋፅኦ ከፍተኛ በመሆኑ ዩኒቨርሲቲዎች አብሮ በመሥራት የሚመጣውን ለውጥ በመገንዘብ ሁላችንም ኃላፊነታችንን ልንወጣ ይገባል ብለዋል።
በፎረሙ ላይ ከሁሉም መንግስት ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንቶች፣ ም/ፕሬዝዳንቶች፣ ከትምህርት ሚኒስቴር እና ከሌሎች ተቋማት የተጋበዙ አመራሮች እየተሳተፉ ይገኛል።