News Detail

የሀገር ውስጥ ዜና
Jun 25, 2024 410 views

በ12ኛ ክፍል ሀገር አቀፍ ፈተና ዙሪያ ከጸጥታ አካላት ጋር ውይይት ተደረገ

በሁሉም የሀገራችን ክፍሎች በዚህ ዓመት በሚሰጠው ሀገር አቀፍ የ12ኛ ክፍል ፈተና ዙሪያ ከጸጥታ አካላት ጋር ውይይት ተደርጓል።
ውይይቱን ያስጀመሩት በትምህርት ሚኒስቴር የአጠቃላይ ትምህርት ልማት ዘርፍ ሚ/ር ዴኤታ ክብርት አየለች እሸቴ እንደገለጹት የ12 ዓመታት ድካም መሰብሰቢያ የሆነው ሀገር አቀፍ የ12ኛ ክፍል ብሄራዊ ፈተና ዙሪያ ውይይት ማድረግ ሊከሰቱ የሚችሉ ክፍተቶችን ለመድፈን ትልቅ እድል ይፈጥራል ብለዋል።
ክብርት ሚኒስትር ዴኤታዋ አክለውም የሀገራችን ትምህርት መልካም ባህላችንን የሚያሳድጉ፣ ለሀገርና ለህዝብ ፍቅር ያላቸው፣ ብዝሃነትን የሚቀበሉ፣ ሰብዓዊ መብቶችን የሚያከብሩ፣ ለሰው ልጅ ደህንነትና እኩልነት ፣ ለፍትህ እና ለሰላምዘብ የሚቆሙ፣ ሁለንተናዊ ስብዕናቸው የተሟላ ዜጎችን ለማፍራት አንዱ መንገድ ግልጽና ከኩረጃ ነጻ የሆነ ፈተናና ምዘና መስጠት ነው ብለዋል። ለዚህም ሁላችንም በምንችለው መጠን አቅማችንን አሟጠን ለስኬታማነቱ እንረባረብ ሲሉ ጥሪ አቅርበዋል።
በውይይት መድረክ ላይ የተገኙት ክቡር የፌዴራል ፖሊስ ኮሚሽን ኮሚሽነር ጄኔራል ደመላሽ ገ/ሚካኤል በበኩላቸው የጸጥታ አካላት በሚመለከታቸው ሃላፊዎቸ በሚሰጥ መመሪያ መሰረት በሙሉ አቅም ተልዕኳቸውን በመፈጸም ሀገራዊ አለኝታነታቸውን ማሳየት ይኖርባቸዋል ብለዋል። የፌዴራል ፖሊስ ምክትል ኮሚሽነር ጄኔራል መላኩ ፋንታ ደግሞ ይህ ስራ በቅንጅት የሚሰራ በመሆኑ ያለምንም ስህተት የተሰጠ ሀገራዊ ተልዕኮን መወጣት ይገባል በማለት በአጽንዖት አስገንዝበዋል።
በውይይቱም በርካታ ሀሳቦች ተነስተው የሀገር አቀፍ ትምህርት ምዘናና ፈተናዎች አገልግሎት ዋና ዳይሬክተር ዶ/ር እሸቱ ከበደ ሰፊ ማብራሪያ የሰጡ ሲሆን ተሰብሳቢዎቹ በሚሰጣቸው መመሪያ መሰረት ተልዕኳቸውን በብቃት ለመወጣት ዝግጁ መሆናቸውን አረጋግጠዋል።
Recent News
Follow Us