News Detail
የአጠቃላይ ትምህርት ዘርፉ ባለፉት አመታት በመጣንበት መንገድ መቀጠሉ አዋጭ ስላልሆነ ወደ ዲጂታል ስርዓት ለመግባት እየሰራን ነው አሉ የትምህርት ሚኒስትሩ ጌታሁን መኩሪያ (ዶ/ር ኢንጂ)።
የአጠቃላይ ትምህርት ዘርፉ ባለፉት አመታት በመጣንበት መንገድ መቀጠሉ አዋጭ አይደለም ያሉት ሚኒስትሩ ወደ ከፍተኛ ቴክኖሎጂ ተጠቃሚነት መሸጋገር ያስፈልጋል ብለዋል።
ለዚህም በዘንድሮው አመት አይነስውራንን ጨምሮ የ12ኛ ክፍል ሀገር አቀፍ ፈተናን በኦንላይን ለመስጠት የተለያዩ ዝግጅቶች እየተደረጉ መሆኑን ገልፀዋል።
የዚህ ዝግጅት አካል የሆነው የአይነ ስውራን ተስማሚ የቴክኖሎጂ ተጠቃሚነት ስልጠና በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ተጀምሯል።
ስልጠናው ለአንድ ወር የሚቆይ ሲሆን ተማሪዎቹ የኮቪድ 19ኝ ወረርሽኝን እየተከላከሉ የኮምፒውተርና የታብሌት መሰረታዊ አጠቃቀምን በማወቅ ከአዲሱ የኦንላይን ቴክኖሎጂ ጋር እንዲተዋወቁ ያደርጋቸዋል።
ይህም ለሚቀጥለው የትምህርት ምዕራፍና የስራ ህይወት ምቹ ሁኔታን ለመፍጠር ያስችላቸዋል ተብሏል።
በዘንድሮው አመት 500 አይነስውራን ተማሪዎች የ12ኛ ክፍል ሀገር አቀፍ ፈተናን ይፈተናሉ።
ከተለያዩ የሀገራችን አካባቢዎች ለተውጣጡ ተማሪዎች የሚሰጠውን የተስማሚ ቴክኖሎጂ ስልጠና የትምህርት ሚኒስቴር፣ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲና የተስማሚ ቴክኖሎጂ ማዕከል ለአይነ ስውራን ናቸው በጋራ የሚሰጡት።
የትምህርት ሚኒስትሩ ጌታሁን መኩሪያ (ዶ/ር ኢንጂ.) ተማሪዎቹ ፈተናውን በኦንላይን መፈተን የሚያስችላቸውን መሰረታዊ የኮምፒውተርና ታብሌት አጠቃቀም ትምህርት ይወስዳሉ ብለዋል።