News Detail

የሀገር ውስጥ ዜና
Aug 22, 2024 287 views

ለተከታታይ 24 ቀናት ሲሰጥ የቆየው የመምህራንና ትምህርት ቤት አመራሮች ልዩ አቅም ግንባታ ስልጠና ተጠናቀቀ!

በያዝነው ክረምት ሲሰጥ የነበረው የመምህራንና የት/ቤት አመራሮች ስልጠና መጠናቀቁን በትምህርት ሚኒስቴር የመምህራንና የትምህርት ቤት አመራሮች መሪ ስራ አስፈፃሚ ዶ/ር ሙሉቀን ንጋቱ ገልጸዋል።
በስልጠናውም መምህራን በሚያስተምሩበት የትምህርት አይነት፣ የማስተማር ስነ-ዘዴ እና በዲጂታል ቴክኖሎጂ ክህሎት ላይ ብቃታቸው ለማሻሻላል ታሳቢ ተደርጎ ለመምህራን የ120 ሰዓታት፣ ለትምህርት ቤት አመራሮች ለ60 ሰዓታት ተሰጥቷል።
ዋና ስራ አስፈጻሚው ስልጠናው በ28 ዩኒቨርስቲዎች ሲሰጥ የቆየ ሞኑን ገልጸው 49505 መምህራንና የትምህርት ቤት አመራሮች፣ 2892 አሰልጣኞች እንዲሁም 224 ዋና አሰልጣኞች እንደተሳተፉበት ተናግረዋል። ስልጠናው በውጤታማነት የተጠናቀቀ ሲሆን ሁሉም ሰልጣኝ መምህራንና ትምህርት ቤት አመራሮች በኦን ላይ የብቃት ምዘና እንዲወስዱ ተደርጓል። የሰልጣኝ መምህራንና ትምህርት ቤት ዳይሬክተሮች የምዘና ውጤት በቀጣይ ይገለጻል ተብሏል።
ይህ የክረምት መርሃ-ግብር በትኩረት ከሚመሩ የትምህርት ሚኒስቴር የሪፎርም ስራዎች አንዱ በመሆኑ በሚቀጥለው ዓመትም የመጀመሪያ ደረጃ መምህራን እና በዚህ ክረምት ስልጠና ያልተሳተፉ የ2ኛ ደረጃ መምህራንን የሚያሳትፍ እንደሆነም ዶ/ር ሙሉቀን ገልጸዋል።
ስልጠናው በአይነቱ የመጀመሪያ በመሆኑ በስልጠናው አሰጣጥ ሂደት የተስተዋሉ አስተዳደራዊና አካዳሚያዊ ተግዳሮቶችን ተለይተው በቀጣይ የመፍትሄ እርምጃ የሚወሰድባቸው እንደሆነም ተገልጿል። የስልጠናው ዋና ግብ የተማሪዎችን ብቃት ማሻሻል በመሆኑ መምህራን በስልጠናው ያገኙትን ልምድ እና እውቀት በመማር ማስተማር ሂደት እንዲተገብሩም አደራ ቀርቧል።
Recent News
Follow Us